Skip to contentSkip to main navigation Skip to footer

News

ባለስልጣኑ በተቋማዊ ባህል፣ በዘላቂ የመንግስት ግዥና በንብረት አወጋገድ ዙሪያ ከሰራተኞች ጋር ተወያየ።

(ነሐሴ 23/2018 ዓ.ም |አዲስ አበባ) — የኢፌዴሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የተቋሙን አሰራር ለማጠናከር፣ የአካባቢ ጥበቃን ያገናዘበ አሰራርን ለመዘርጋት እና የስራ ቦታ ፕሮቶኮልን ለማሻሻል የሚያስችሉ ሶስት ዋና ዋና ሰነዶችን መሰረት በማድረግ ከሰራተኞቹ ጋር የውይይት መድረክ አካሄዷል።

የውይይት መድረኩን በንግግር የከፈቱት የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሰረት መስቀሌ እንደገለጹት ተቋሙ የተጣለበትን ሀገራዊ ሀላፊነት በብቃት ለመወጣት ጠንካራ ተቋማዊ ባህል መገንባትና ዘመናዊ የአሰራር ስልቶችን መከተል ወሳኝ መሆኑን ያመላከቱ ሲሆን የሚዘጋጁ አሰራሮችና ማኑዋሎች ወደ ተግባር የሚቀየሩት በሰራተኛው ሙሉ ተነሳሽነት እና ቁርጠኝነት በመሆኑ መሰል የውይይት መድረኮች ያላቸውን ከፍተኛ ሚና አጉልተው አሳይተዋል።

ተቋማዊ ባህል፣ አለባበስና ፕሮቶኮል የውስጥ መመሪያ ላይ ገለጻ ያቀረቡት በባለስልጣኑ የኢጂፒ ፕሮጀክት ማናጀር አቶ ያፌት መኮንን ሲሆኑ መመሪያው የተቋሙን በጎ ገጽታ የሚገነቡ የሙያ ስነ-ምግባር መርሆች፣ የስራ ቦታ አለባበስ ስታንዳርዶች እና የፕሮቶኮል ስርዓቶችን በጥንቃቄ መተግበር እንደሚገባ አመላክተዋል።

በሌላ በኩል ዘላቂነት ያለው የመንግስት ግዥን በሚመለከት የባለስልጣኑን የሦስት አመት እቅድ ያቀረቡት በመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የማሻሻያ እና አቅም ግንባታ መሪ ስራ አስፈጻሚ በአቶ መላኩ ተጓዴ የቀረበ ሲሆን የመንግስት ግዥ አሰራር ከኢኮኖሚያዊ ጥቅም ባሻገር የአካባቢ ጥበቃንና የማህበራዊ ሀላፊነትን ያገናዘበ (Green Public Procurement) እንዲሆን የሚያስችሉ ስልታዊ አቅጣጫዎችን መከተል እንዳለበት አመላክተዋል።

አቶ መላኩ ከዘላቂ የመንግስት ግዥ እቅድ በተጨማሪ በጤናና በአካባቢ ጉዳት ሊያስከትሉ የሚችሉ ከአገልግሎት ውጪ የሆኑ ንብረቶች አያያዝ፣ አጠባበቅ እና አወጋገድ ማኑዋል ላይ ገለጻ አቅርበዋል። አቶ መላኩ በገለጻቸው ከአገልግሎት ውጪ የሆኑና ለጤናም ሆነ ለአካባቢ ስጋት የሚደቅኑ ሀብቶችን በአስተማማኝ ሁኔታ ለመያዝ፣ ለመጠበቅና ለማስወገድ ባለስልጣኑ ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ጥናት እንዳስጠና እና ጥናቱን ተከትሎም የአፈጻጸም ማኑዋል እንዳዘጋጄ ገልጸው እነዚህን ንብረቶች በሰው ጤናም በአካባቢ ላይ ጉዳት ሳያደርሱ ማስወገድ እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል።

ከሰነዶቹ መቅረብ በኋላ ከተሳታፊ ሰራተኞች ጥያቄዎችና አስተያየቶች ተነስተው ውይይት ተደርጎባቸዋል።

የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም በክልሎች በውጤታማነት እንዲተገበር የተቀናጀ ድጋፍ እና ክትትል አስፈላጊ መሆኑ ተገለጸ።

(ነሐሴ 14/2018 .)– የኢፌዴሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የባለስልጣኑን የመንግስት የአገልግሎትና አስተዳደር የሪፎርም አፈጻጸምን በሚመለከት ለክክልል ፋይናንስ እና ግዥ ሀላፊዎች ልምድ የማከፈልና የውይይት መድረክ አካሂዷል።

መድረኩን በንግግር የከፈቱት የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሰረት መስቀሌ በንግግራቸው የሪፎርም ስራው ዋና አላማ ግልጽነትን፣ ብቃትና ውጤታማነትን ያረጋገጠ አካታች የሲቪል ሰርቪስ ስርዓት መገንባት መሆኑን አመላክትዋል። ክብርት ወ/ሮ መሰረት አክለውም ባለስልጣኑ የሪፎርም የዝግጅት ምዕራፍን በውጤታማነት አጠናቆ ወደ ትግበራ ምዕራፍ እንደተሸጋገረ እና በአሁኑ ወቅት ወደ ማጽናት ምዕራፍ ለመሸጋገር በትጋት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

ክብርት ወ/ሮ መሰረት በንግግራቸው ባለስልጣኑ ሁሉንም የአገልግሎት አሰጣጥ ዲጂታል የማድረግ ስራ ማከናወኑንና አብዛኞቹ የአሰራር ስርዓቶች በውስጥ አቅም የተሰሩ በመሆናቸው የመንግስትን ሀብት የመቆጠብና የሰራተኞችን አቅም የማበልጸግ እድል መፍጠራቸውን ጠቁመዋል። ሪፎርሙ ውጤታማ የሚሆነው በአንድ ተቋም ብቻ ሳይሆን ሁሉን አቀፍ እና አካታች ሆኖ ሲተገበር በመሆኑ የክልል አመራሮችም የላቀ ቁርጠኝነት በማሳየት ልምድ እና ምርጥ ተሞክሮዎችን ማስፋት እንደሚገባቸውም አሳስበዋል።

በመድረኩ የባለስልጣኑ የአገልግሎትና አስተዳደር የሪፎርም አፈጻጸም ሪፖርት በመንግስት ግዥና ንብረት ማሻሻያ እና አቅም ግንባታ መሪ ስራ አስፈጻሚ አቶ መላኩ ተጓዴ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል።

በሌላ በኩል በፌዴራል ደረጃ እየተተገበረ የሚገኘው የሪፎርም ስራ ውጤታማነት በክልሎች እና በከተማ አስተዳደሮች ሳይደበዝዝ በተመሳሳይ ሁኔታ እንዲተገበር በባለስልጣኑ የሚሰጠውን ሙያዊ ድጋፍ፣ የስልጠና እና የክትትል ስራዎች አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ከተሳታፊዎች ተነስቷል።

በመጨረሻም ክልሎች አዳዲስ ህጎችን ማውጣት ሳይጠበቅባቸው ባለስልጣኑ ያዘጋጃቸውን አሰራሮች ከነባራዊ ሁኔታቸው ጋር አጣጥሞ መጠቀም የሚችሉ መሆናቸውንና ባለስልጣኑ የስልጠና፣ የምክር እና ተያያዥ ድጋፎችን እንደቀድሞው ሁሉ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የባለስልጥኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሰረት አረጋግጠዋል።

የኢፌዴሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የቅደመ መደበኛ ትምህርትቤት ግንባታን በይፋ አስጀመረ።

(ነሐሴ 06 ቀን 2018 ዓ.ም) አዲስ አበባ — የኢፌዴሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን በክረምቱ ወራት ከአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጎን ለጎን አረጋውያንንና አቅመ ደካሞችን ከመመገብና የቁሳቁስ ድጋፍ ከማድረግ ባለፈ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የቅድመ መደበኛ የትምህርት ቤት ግንባታን በይፋ አስጀምሯል።

ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ካማሺ ዞን ሰዳል ወረዳ በሚገኘው ዲዛ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ውስጥ ሰባት ክፍሎች ያሉት አዲስ የትምህርት ቤት ግንባታ ያስጀመረ ሲሆን በእለቱ ለ100 ተማሪዎች የተመሪ ቦርሳን ጨምሮ ሙሉ የትምህርት ቁሳቁስ እርዳታ አበርክቷል።

በመርሃ ግብሩ ላይ የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሰረት መስቀሌ፣ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ዚያድ አብዱላሂ፣ የሰዳል ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ፈረንጂ አባኬሻ፣ የባለስልጣኑ የስራ ኃላፊዎች እንዲሁም ሌሎች የክልልና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።

የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሰረት በእለቱ ባስተላለፉት መልዕክት እንደገለጹት መንግስት አቅመ ደካሞችን ከማገዝ ባሻገር የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን በፅኑ መሰረት ላይ የመገንባት ስራ እየሰራ እንደሚገኝና ባለስልጣን መስሪያ ቤቱም ሰው ተኮር ተልዕኮን አንገብጋቢ አድርጎ በመያዙ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው የማህበረሰብ ክፍሎች በተለያዩ ጊዜያት ማህበራዊ ኃላፊነቱን ሲወጣ መቆየቱን ገልጸዋል።

ዋና ዳይሬክተሯ አክለውም “እዚህ የተገኘነው ህብረተሰቡን ለማየትና ለማዳመጥ፣ ተማሪዎችን ለማገዝ፣ ለነገ ሀገር ተረካቢ ትውልድ ማደጊያ የሚሆን ትምህርት ቤት ለመገንባት እና ከማሀበረሰባችን ጋር በመሆን ችግኝ ለመትከል ነው” ብለዋል። የትምህርት ቤቱ ግንባታው በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ለተማሪዎች አገልግሎት መስጠት እንዲጀምር የክልሉ እና የወረዳው አመራሮች ቅርብ ክትትል እንዲያደርጉ አደራ ያሉት ክብርት ወ/ሮ መሰረት ማህበረሰቡ ሕፃናትን የመንከባከብ፣ ሴቶችን የመደገፍ፣ ወጣቶችን የማሰራት እና ውቧን አካባቢ የበለጠ የማስዋብ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።

በሌላ በኩል የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ዚያድ አብዱላሂ በበኩላቸው በክረምቱ ወራት መንግስት የተለያዩ የበጎ ፈቃድ ስራዎችን በማከናወን ወደ ህዝቡ ይበልጥ እየቀረበ እንደሚገኝ ገልፀው፣ ክልሉም በመሰል በጎ አድራጎቶች ላይ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። አክለውም ክልሉ እየተነቃቃ የመጣውን ኢኮኖሚ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ዘርፈ ብዙ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

በአማራ ክልል የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትን (e-GP) ተግባራዊ ለማድረግ የዝግጅት ሥራዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል።

(ነሀሴ 05/2018 ዓ.ም)፣ ባህር ዳር — በኢፌዴሪ የመንግሥት ግዥ እና ንብረት ባለሥልጣን እና በአማራ ክልል ገንዘብ ቢሮ ትብብር የሚሰጠው የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት (e-GP) የሥልጠና ፕሮግራም በባህር ዳር ከተማ መካሄድ ጀምሯል። ሥልጠናው በ2019 ዓ.ም አዲሱን አሠራር በክልሉ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ ታስቦ ለተመረጡ አስር የክልሉ ተቋማት የሥራ ኀላፊዎች እና የግዥ ባለሙያዎች እየተሰጠ የሚገኝ ነው።

የአማራ ክልል ገንዘብ ቢሮ ኀላፊ አቶ አታላይ ጥላሁን በስልጠናው ወቅት እንደገለጹት የመንግስት አሠራርን በዲጂታል ቴክኖሎጂ የማዘመንና አገልግሎት አሰጣጥን ውጤታማ የማድረግ ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ይገኛሉ። የሕዝብ ሃብትን በቁጠባ እና በተቀላጠፈ መልኩ ለማስተዳደር የሚያስችለውን አዲሱን የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት በ2019 ዓ.ም በክልሉ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ የሕግ ማዕቀፍ፣ የመመሪያ እና የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ዝግጅቶች እየተደረጉ እንደሆነም አብራርተዋል። አክለውም የአስሩ ተቋማት የሙከራ ትግበራ ስኬታማነት በመገምገም ሥርዓቱን እስከ ታችኛው የመንግሥት እርከን ለማስፋት ትልቅ መሠረት መሆን እንዳለብት አመላክተዋል።

በመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ፕሮጀክት የአቅም ግንባታ አስተባባሪ አቶ ደበበ ማሞ እንደገለጹት በበኩላቸው ባለስልጣኑ የአገልግሎት አሰጣጡን ጥራት፣ ግልጽነት እና ቅልጥፍናን በከፍተኛ ደረጃ ለማሳደግ የአሠራር ሥርዓቱን ሙሉ በሙሉ ዲጂታል የማድረግ ስራ እየሰራ እንደሚገኝ ያብራሩ ሲሆን የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት በ2014 ዓ.ም በዘጠኝ የፌዴራል ተቋማት በሙከራ ደረጃ ተጀምሮ በአሁኑ ወቅት በሁሉም የፌዴራል ተቋማት፣ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች እና ዩኒቨርሲቲዎች ሙሉ በሙሉ እና ውጤታማ በሆነ መልኩ እየተተገበረ እንደሚገኝ አብራርተዋል።

አቶ ደበበ አክለውም አሠራሩ ከወረቀት እና ከሰው ንኪኪ ነፃ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀ እና አስተማማኝ በመሆኑ ወጥ የሆነ ሀገራዊ አሠራር ለመዘርጋት ሥርዓቱን ወደ ክልሎች የማውረድ ሥራ በስፋት እየተሠራ መሆኑንና ተመሳሳይ የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎች ለሌሎች ክልሎችም እየተሰጡ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በተጨማሪም አብዛኞቹ ክልሎች የየራሳቸውን የግዥ ሕግ ከፌዴራሉ የግዥ ሕግ ጋር የማጣጣም እና የማስማማት ሥራዎችን በስፋት እያከናወኑ እንደሚገኙ ጠቁመዋል።

በሥልጠናው እየተሳተፉ የሚገኙ የግዥ ባለሙያዎች በበኩላቸው እስካሁን የነበረው ወረቀትን መሠረት ያደረገ አሠራር የተንዛዛ፣ ለአሠራር ግልጽነት አጠራጣሪ እና አሰልች እንደነበር ገልጸው የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓቱ መተግበሩ ጊዜን፣ ጉልበትን እና ወጭን ከመቆጠቡ ባሻገር ሙስናን በመከላከል እና እንግልትን በማስቀረት አገልግሎቱን በከፍተኛ ሁኔታ ያቀላጥፋል ብለዋል።

በመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ባለሙያዎች እና አስተባባሪዎች እየተሰጠ የሚገኘው ይህ አቅም የመገንባት ሥልጠና ለሚቀጥሉት ቀናት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ታውቋል።