(መጋቢት 22/2018 ዓ/ም)፣ የኢፌዴሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን አመራርና ሰራተኞች የ2018 በጀት ዓመት የ9 ወራት እቅድ አፈጻጸምን በጋራ ገምገመዋል፡፡
ባለስልጣኑ ከተቋማዊ አቅም ግንባታ፣ ከመንግስት ግዥና ንብረት ዲጅታላይዜሽን፣ ከዘለቄታዊነት የግዥና /Sustainable Procurement/ ንብረት አስተዳደር ሥርዓት ማጎልበት፣ ከመንግስት ግዥና ንብረት አገልግሎት እና መረጃ ጥራትና ሽፋን ማሳደግ፣ ከመንግስት ግዥና ንብረት የፖሊሲ፣ ማማከር አገልግሎት እና የጥናትና የምርምር፣ ከመፈፀምና ማስፈፀም አቅም ግንባታ፣ ሙያዊ ድጋፍ፣ ክትትል የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ከመስጠት፣ ከስትራቴጂያዊ የቴክኒክ ትብብር እና አጋርነትን ከማጠናከር፣ ከመንግስት ግዥና ንብረት ኦዲትና ክትትል ሥራዎችን ጥራትና ሽፋን ከማሳደግ እንዲሁም ከግዥ አፈፃፀም እና ንብረት ሽያጭ ላይ የሚቀርቡ የይግባኝና የጥፋተኝነት ውሳኔ አሰጣጥን ከማጠናከር አንጻር የተቋሙን አፈጻጸም በጥልቀት ገምግሞ የቀጣይ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል፡፡
ባለስልጣኑ የአሰራር ስርዓቱን ጥራትና ቅልጥፍና ለማሳደግ አዋጁን ጨምሮ መመሪያዎችንና ሌሎች የአሰራር ስርዓቶችን ውጤታማ በሆነ መንገድ ተግባራዊ ያደረገ ሲሆን ከዲጂታላይዜሽን አንጻርም የመንግስት ኤሌክትሮኒክ ግዥ (e-GP)፣ የተሸከርካሪ ስምሪት፣ ነዳጅ አጠቃቀም ሥርዓት (Fleet Management System)፣ የበየነ መረብ ትምህርት (e- learning) እና ሌሎች ዲጂታል አገልግሎቶችን እየተገበረ እንደሚገኝ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡
ተቋሙ በትኩረት እየተገበራቸው ከሚገኙ አበይት ዲጂታል ተግባራት አንዱ የመንግስት ኤሌክትሮኒክ ግዥን (e-GP) ወደ ክልሎች ማውረድ መሆኑንና ቀድመው የጀመሩትን አዲስ አበባ ከተማ መስተዳደርና ኦሮሚያ ክልልን ከመደገፍ በተጨማሪ ለደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ ለደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል፣ ለማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣ ለሶማሌ ክልል፣ ለአማራ ክልል እና ለድሬዳዋ ከተማ መስተዳደር ስርዓቱን ሊተገብሩ በሚችሉብት ሁኔታ ላይ የአቅም ግንባታ ሥልጠና እና የቴክኒክ ድጋፍ መሰጠቱም ተብራርቷል፡፡
በሪፖርቱ ከተብራሩና ተቋሙ በትኩረት ከሚያከናውናቸው አበይት ተግባራት አንዱ የኦዲት ስራ ሲሆን በ9 ወራት በ56 ተቋማት ላይ የህጋዊነት ኦዲት (93.3%)፣ በ38 ተቋማት ላይ የክትትል ስራ (100%)፣ በ13 ተቋማት ላይ የጥቆማ ኦዲት (100%) እንደተከናወነ በሪፖርቱ ተካትቷል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ይግባኝና ጥፋተኝነትን በሚመለከት በ9 ወራት ውስጥ 174 የጥፋተኝነት ሪፖርት መረጃ ተሟልቶላቸው ለባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የቀረቡ ሲሆን 167 (95.97%) ውሳኔ እንዲያገኙ ተደርጓል:: በሌላ በኩል ይግባኝን በሚመለከት በ9 ወራት ውስጥ መረጃ ተሟልቶላቸው ከቀረቡ 101 ይግባኝ ውስጥ 98 (97%) ውሳኔ እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡
በመጨረሻም የሪፎርም ስራዎችን አጠንክሮ ማስቀጠል፣ የድጋፍና ስልጠና ስራዎችን ማጠናከር፣ የመንግስት ኤሌክትሮኒክ ግዥን ወደ ክልሎች ለማውረድ ተጨማሪ ስራ መስራት እንደሚያስፈልግ በዋና ዳይሬክተሯ ክብርት ወ/ሮ መሰረት አቅጣጫ ተቀምጦ ግምገማው ተጠናቋል፡፡






