Skip to contentSkip to main navigation Skip to footer

Author: Yonas Habesha

ባለስልጣኑ የስልጠና አሰጣጥን ወደ ላቀ ደረጃ ማሳደግ የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመ።

(ሰኔ 09/2018 ዓ.ም)፣ የኢፌዴሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የግዥና ንብረት ፕሮፌሽናላይዜሽን ስልጠናን ከፍ ለማድረግ ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል። የመግባቢያ ስምምነቱ የግዥና ንብረት አስተዳደር የሙያ ማሻሻያ ስልጠና ፕሮግራምን በጋራ ተግባራዊ ለማድረግ የሚያግዝ ሲሆን የግዥና ንብረት ባልሙያዎችን በስነ- ምግባር የታነጹ እንዲሁም ሁለንተናዊ አቅምን፣ ሙያዊ ብቃትን እና አፈፃፀምን ለማሳደግ የሚያግዝ መሆኑ ተገልጿል።

በፊርማ ስነ- ስርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሰረት መስቀሌ እንደገለጹት ስምምነቱ በመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን እና በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ መካከል የተመሰረተ የስትራቴጂክ ትብብር ምልክት ሲሆን በኢትዮጵያ የመንግሰት ግዥ እና ንብረት አስተዳደር ስርዓት ላይ ብቃት ያለው ባለሙያ ለማፍራት የተደረገ አስፈላጊ እርምጃ መሆኑን አመላክተዋል።

ክብርት ወ/ሮ መሰረት አያይዘውም የትብብር ስምምነቱ ዋና ዓላማ ባለሙያዎችን ማብቃትና ማሻሻል፣ የግዥ ሕጎችን በትክክል ማስፈጸም የሚችሉ ባለሙያዎች ማፍራት፣ ግልፅነት፣ ተጠያቂነት እና ብቃት ያለው የሀብት አጠቃቀም ማሳደግ፣ በመንግስት ተቋማት ውስጥ የተደራጀ የስልጠና ስርዓት ማቋቋም መሆናቸውን አብራርተዋል።

ክብርት ዋና ዳይሬክተሯ የግንኙነትና የስራ ሰንሰለቱን ሲያብራሩ የኢፌዴሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ፕሮግራሙ ላይ የፖሊሲ አቅጣጫ መስጠት፣ የስልጠና ይዘት ማዘጋጀት፣ ሰልጣኞችን እና አሠልጣኞችን መምረጥ፣ የግምገማ ሂደት መምራት እና ሰርተፊኬት መስጠትን በሚመለከት በከፍተኛ ሀላፊነት የሚሰራ ሲሆን አዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በበኩሉ እንደ ዋና የአካዳሚክ ተቋም የስልጠናውን ዕለታዊ አስተዳደር፣ የመማሪያ አካባቢ አቅርቦት፣ የሠልጣኝ ሁኔታ ክትትል እና በሁሉም ሂደቶች ባለስልጣኑን በማማከር  በኩል በከፍተኛ ትጋት ሀላፊነቱን እንደሚወጣ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዘዳንት ደረጄ (ዶ.ር) በበኩላቸው ስምምነቱን እውን የሚያደርጉ ስራዎች አስቀድሞ ሲሰሩ መቆየታቸውን አውስተው ስምምነቱ ሁለንተናዊ ብቃትን የተላበሰ የግዥና ንብረት ባለሙያ ለመፍጠር እንደሚያግዝ አብራርተዋል።

የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዘላቂ የመንግስት ግዥ አተገባበርን በብቃት ለመወጣት ምን እያከናወነ ነው?

እንደሚታወቀው የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የአሰራር ስርዓቱን በማዘመን በአፍሪካ አርዓያ ከሆኑ የመንግስት ግዥና ንብረት ተቆጣጣሪ ተቋም የመሆን ራዕይን ቀርጾ በትጋት የሚሰራ ተቋም ነው፡፡ በዚህም ሁሉንም የአገልግሎት አሰጣጥ ዲጂታል ማድረግ ችሏል፡፡ በተለይም የመንግስት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓት ሀገራችን የያዘችውን ዲጂታል ኢኮኖሚ በመደገፍ በኩል ያለው ሚና ላቅ ያለ ነው፡፡ ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ ባለስልጣኑ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ የሪፎርም የትግበራ ምዕራፍን በብቃት እየተወጣ የሚገኝ ተቋም ነው፡፡ በዚህ የሪፎርም የዝግጅት ምዕራፍ ብዙ የአሰራር ስርዓቶች የተቀረጹ ሲሆን በትግበራ ምዕራፉ ደግሞ የአሰራር ስርዓቶችን ስራ ላይ አውሏል፡፡

ስለሆነም በዚህ  የዝግጅትና የትግበራ ምዕራፍ ከተከናወኑ ተግባራ አንዱ ቀጣይነት ያለው የመንግስት ግዥ (Sustainable Public Procurement manual) ማዘጋጀት ሲሆን ማኑዋሉ ተዘጋጅቶ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት የማድረግ ና ስልጠና የመስጠት ስራ እየተከናወነ ይገኛል፡፡ በመሆኑም እንደ ሀገር ዘላቂ የግዥ አሠራሮች የኢንዱስትሪ ልማት የሚያረጋግጡ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራን የሚያበረታቱ፣ በአካባቢ ላይ ጉዳት የማያደርሱ፣ ድህነትን ቅነሳ ላይ ትኩረት የሚያደርጉ፣ የሀገሪቱን አረንጓዴ ኢኮኖሚ ወይም ዲጂታል ኢኮኖሚ እንዲደግፉ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል፡፡

ዘላቂነት ያለው የመንግስት ግዥን (Sustainable Public Procurement) በሚመለከት በፌዴራል ግዥና ንብረት አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 1333/2016 አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ አንድ  የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች እንደ ግዥው ባህርይ ከአካባቢ ብክለት የፀዳ፣ መልሶ መጠቀምን፣ የህይወት ዘመን ወጪ ትንተናን እና የማህበረሰብ ተጠቃሚነትን ከግምት ያስገባ ዘላቂነት ያለው የግዥ አፈፃፀም አሰራርን በፍላጎት መግለጫ፣ በመገምገሚያ መስፈርት፣ በውል ቃላትና ሐረጎች ዝግጅት ወቅት፣ እንዲሁም በውል አፈፃፀም ቁጥጥር ወቅት ተግባራዊ መደረግ እንዳለባቸው ያብራራል፡፡

በተመሳሳይ ይህን አዋጅ ለማስፈጸም በወጣው የፌዴራል መንግስት የግዥ አፈጻጸም መመሪያ ቁጥር 1073/2017 ክፍል ሰባት ላይ ዘላቂነት ያለው የግዥ ስርዓትን ተፈጻሚ ማድረግ እንደሚያስፈልግ በተለይም ግዥው የህይወት ዘመን ወጪ ትንተና የሚሰራለት፣ የአካባቢ ጥበቃን ታሳቢ ያደረገ እና የማህበረሰብ ተጠቃሚነትን ታሳቢ ያደረገ መሆን እንዳለበት ያብራራል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ባለስልጣኑ አዋጁንና መመሪያውን ሳይሸራረፍ መፈጸም ይቻል ዘንድ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናዎችን ከመስጠት ጀምሮ ዘርፈ ብዙ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል፡፡

የዘላቂ የመንግስት ግዥ ዋና ዋና መርሆች (principles of sustainable procurement) ምንድን ናቸው?

ዘላቂ የመንግስት ግዥ የሚመራባቸው በርካታ መርሆች አሉት። ከእነዚህ ውስጥ፦

 

ግልጽነት (Transparency)፦ የሚከናወኑ የግዥ ሂደቶች ለሁሉም ተሳታፊዎች ግልጽ እና ክፍት መሆን አለባቸው። ግልጽነት ሙስናን ይቀንሳል በምትኩ የህዝብን እምነት ለማሳደግ ከፍተኛ ሚና አለው።

 

ተጠያቂነት (Accountability)፦  ግዥውን በበላይነት የሚመሩት ሀላፊዎችም ይሁኑ ግዥውን የሚፈጽሙት ባለሙያዎች  በግዥ ውሳኔዎች እና በግዥ ክንውኖች ላይ ኃላፊነት ሊወስዱ ይገባል፤ በተለይም የተቋም የበላይ ሀላፊዎች  የመንግስት ሀብት በብቃት እና በተፈለገው መንገድ ጥቅም ላይ ስለመዋሉ ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል።

 

ፍትሃዊ ውድድር (Fair Competition)፦ ሁሉም አቅራቢዎች/ተጫራቾች ለመንግስት ውሎች ለመወዳደር እኩል ዕድል ሊኖራቸው ይገባል።

 

ለተከፈለው ገንዘብ ተመጣጣኝ ዋጋ (Value for Money)፦ ዘላቂነት ያለው የመንግስት ግዥ ትኩረት በዝቅተኛው የመግዣ ዋጋ ብቻ ሳይሆን በሙሉ የህይወት ዑደት ወጪ (whole-life costing) ላይ የሚያተኩር በመሆኑ የሚከናወነው ግዥ ይህን መሰረት ያደረገ መሆን ይኖርበታል።

የአካባቢ እና ማህበራዊ ኃላፊነት (Environmental and Social Responsibility)፦ የግዥ ውሳኔዎች እና የሚከናወኑ ግዥዎች በአካባቢ ላይ የሚደርሰውን ጉዳት የሚወንሱ እና ማህበራዊ ጥቅሞችን ማሳደግ የሚችሉ አለባቸው።

ዘላቂ የመንግስት ግዥ (Sustainable Public Procurement) ሦስት ዋና ዋና ጉዳዮችን ታሳቢ ያደረገ ነው ሲባል ምን ማለት ነው?

ዘላቂ የመንግስት ግዥ (Sustainable Public Procurement) ከአንድ አቅጣጫ ብቻ የሚታይ አይደለም፡፡ ማለትም ግዥውን ለመፈጸም ዝቅተኛ ዋጋን እንደ መስፈረት መውሰድ በቂ አይደለም፤ የእቃውን ጥራትም እንደ ግዥ መስፈርት ወስዶ ግዥውን መፈጸም በቂ አይደለም፡፡ ይልቁንም ግዥውን ለመፈጸም ከላይ ከገለጸናቸው መስፈርቶች በተጨማሪ ያለውን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሚታ፣ በአካባቢ ላይ ተጽዕኖ የማያሳድር መሆኑ፣ ማህበራዊ አገልግሎት ላይ ያለው አስተዋጽዖ፣ አረንጓዴ ልማትን መድገፍ የሚያስችል መሆኑና ሌሎች መሰል መስፈርቶች ከግምት ውስጥ የሚገቡ ናቸው፡፡ በዝርዝር ለመመልከት ያህል፦

የኢኮኖሚ ዘላቂነት (Economic sustainability) የኢኮኖሚ ዘላቂነት በምርቶች እና በአገልግሎቶች የህይወት ዑደት ውስጥ ለተከፈለው ገንዘብ ተመጣጣኝ ዋጋ (Value for Money) ማረጋገጥ ላይ ያተኩራል። ይህም የወጪ ውጤታማነትን (Cost efficiency)፣ የጥራት ማሻሻያን (Quality improvement)፣ ዘላቂነትን (Durability)፣ የጥገና ወጪ መቀነስን  (Reduction of maintenance costs) እና የረጅም ጊዜ የፋይናንስ ቁጠባን (Long-term financial savings) መሰረት ያደረገ ነው፡፡ ስለሆነም በዚህ ሂደት ውስጥ የግዥ ባለሙያዎች የመግዣ ዋጋ ላይ ብቻ  አያተኩሩም ይልቁንም ከመግዣ ዋጋው በተጨማሪ የሥራ ማስኬጃ ወጪዎችን፣ የጥገና ወጪዎችን እና የማስወገጃ ወጪዎችንም ግንዛቤው ውስጥ ያስገባሉ።

የአካባቢ ዘላቂነት (Environmental sustainability) የአካባቢ ዘላቂነት የግዥ ሂደቶች ግዥው በአካባቢ ላይ የሚያስከትለውን አሉታዊ ተፅዕኖ መቀነስ ላይ ያተኩራል። ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርነው የሚገዙ ግዥዎች በአካባቢ ላይ ብክለትን የማያስከትሉ መሆናቸው መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ ይህን ስንል የሚገዙ ምርቶች ብክለትን የሚቀንሱ፣ ኃይልን የሚቆጥቡ፣ እንደገና ጥቅም ላይ ሊውሉ የሚችሉ ቁሳቁሶችን የሚጠቀሙ፣ የግሪን ሀውስ ጋዞችን የሚቀንሱ እና ታዳሽ ኃይልን የሚያበረታቱ መሆናቸው ግንዛቤ ውስጥ መግባት ይኖርበታል፡፡ ምክንያቱም የአካባቢ ተስማሚ ግዥ (Environmental Sustainability Procurement) የአየር ንብረት ለውጥን ለመቀነስ እና የተፈጥሮ ሀብቶችን ለመጠበቅ አስተዋፅኦ ያደርጋል።

ማህበራዊ ዘላቂነት (Social Sustainability):- ማህበራዊ ዘላቂነት የማህበራዊ ደህንነትን ለማሻሻል እና ሥነ-ምግባራዊ የንግድ አሠራሮች ማረጋገጥ ላይ የሚያተኩር ሲሆን ፍትሃዊ የሥራ ልምዶች፣ የሰብአዊ መብቶች ጥበቃ፣ የሥራ ቦታ ደህንነት፣ የፆታ እኩልነት፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ለተጋላጭ ቡድኖች ድጋፍ መስጠትን የሚያበረታታ ነው፡፡