Skip to content Skip to main navigation Skip to footer

General

በኤሌክትሮኒክ የመንግስት ግዥ ሥርዓት ዙሪያ ከባንኮች እና ኢንሹራንሶች ጋር የውይይት መድረክ ተካሄደ፡፡

(ሰኔ 5/2017 ዓ/ም) ባለስልጣኑ በኤሌክትሮኒክ የመንግስት ግዥ ሥርዓት ዙሪያ በርካታ ተግባራትን ከተለያዩ ተቋማት ጋር በትስስር ተግባራዊ እያደረገ እና አሰራሩን ይበልጥ እያዘመነ ለዲጅታል ኢኮኖሚ ዘርፉ ሃገራዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ በአዋጅ የተሰጠውን ተግባር እና ኃላፊነት እየተወጣ ይገኛል፡፡

ይህንን ተከትሎ ከባንኮች እና ኢንሹራንሶች ጋር በጋራ መስራት የሚገባ ተግባር በመሆኑ ቀደም ሲል ሲስተሙን አስተሳስሮ ለመተግበር ባለስልጣኑ መድረክ የፈጠረ ቢሆንም ተግባራዊነቱ ተጠናክሮ ባለመቀጠሉ ዳግም ተወያይቶ ለትስስሩ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር ታስቦ በካፒታል ሆቴል የተዘጋጀ መድረክ ነው፡፡

መድረኩን የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሰረት መስቀሌ የከፈቱ ሲሆን ከመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ጋር ተያያዥ ገለጻ በመስጠት የግዥ ስርዓቱ የደረሰበትን አጠቃላይ ሁኔታ፣ ያስገኛቸው ጠቀሜታዎች፤በትግበራ ወቅት ያጋጠሙ ተግዳሮቶችና አስቻይ ሁኔታዎችን በገላጻቸዉ ወቅት አካተዋል፡፡

የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂን የገለጻቸው አካል ያደረጉት ዋና ዳይሬክተሯ በዚህ ረገድ ባንኮች እና ኢንሹራንሶች ግንባር ቀደም ሚና ከሚጫወቱ ተቋማት መካከል መሆናቸውን አስታውሰው የዲጅታል ሽግግር ጉዞ ማሳያ ከሆኑት መካከል አንዱ የሆነውን የኤሌክትሮኒክ ግዥ አፈጻጸም ሥርዓትን በመተግበር ሂደት የሲስተም ትስስር ሊፈጥሩ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

በመቀጠልም በግዥ ሂደት ሲስተሙ የሚያተናግዳቸው ትግባራዎች በዝርዝር በማመላከት ከነዚህም መካከል መረጃዎችን በቀላሉ ማግኘት እንዲቻል፤ከአቅራቢዎች ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ካላቸው ተቋማት ጋር የሲስተም ትስስር መደረጉን አስታውሰው በቀጣይ በኢጂፒ ሲስተም በኩል ብቻ ግዥ መፈጸም እንዳለበት የሚደነግገው ህግ ተፈጻሚነት በማረጋገጥ በመንግስት ግዥ ላይ የሚስተዋለውን የውስንነት ችግር ለመፍታት እና ከእጂ ንክኪ የጸዳ ለማድረግ ብሎም ደህንነቱ የተጠበቀ የደንበኞችን እርካታ የሚያረጋግጥ የዘመነ የአሰራር ስርዓት መዘርጋት ተገቢ ስለሆነ በትስሰር ሊተገበር እንደሚገባ ገልጸው ስርዓቱን ተጠቅመው ባንኮች እና ኢንሹራንሶች የሚያከናውኗቸውን ተግባራት በግልጽ ተገንዝበው በሲስተሙ መተግበር እንደሚገባቸው አብራርተዋል፡፡

ዋና ዳይሬክተራ በገለጻቸው በዚሁ የግዥ ስርዓት በርካታ የገንዘብ ቁጥር ያለዉ ግዥ የሚፈጸም እና በሂደቱም ዋስትና የሚጠየቅባቸው በሲስተሙ በፈሰሱ ጨረታዎች ልክ የሚሆንበት አሰራር በወረቀት ሊተገበር ስለማይገባ አስተማመኝ እና ደህንነቱ የተጠበቀ ዋስትና በሲስተም ሊታሰርለት ይገባል ብለዋል፡፡ ባንኮችና ኢንሹራንሶችም መሰል ጉዳዩችን በበይነ በርብ አለማድረጋቸው የተፈለገውን ዓላማ ከግብ ለማድረስ እንቅፍት ስለሆነ ይህን ተፈጻሚ ማድረግ የሚያስችል ስምምነት ላይ ለመድረስ እና ሂደቶች ሳይዛነፉ እንዲተገበሩ ለማድረግ ውይይቱ ማስፈለጉን ገልጸዋል፡፡

በመቀጠልም የሲስተም ትስስሩ በባንኮች እና ኢንሹራንሶች እንዴት ተፈጻሚ እንደሚሆን የሲስተሙን ሂደት በግልጽ ያመላከተ ገለጻ በቪዲዩ በማስደገፍ በአልሚው ድርጅት/ፔራጎ/ ከፍተኛ ባለሙያ በአቶ ኤልያስ ጥበቡ አማካኝነት ለተሳታፊዎች ቀርቧል፡፡

የቀረበውን የውይይት መነሻ ሃሳብ መሰረት በማድረግ ተሳታፊዎች አስተያየት የሰጡ ሲሆን ባለስልጠኑ የግዥ ስርዓቱን ለማዘመን የሄደበትን እርቀት አድንቀው የሲስተም ትስስሩን በተመለከተ በአዎንታዊ ጎኑ የተቀበሉት እና ለመተግበርም ዝግጁነታቸውን የገለጹ ሲሆን ተገቢውን ቴክኒካል ስልጠና ከማግኘት አንጻር፤ከደንበኞቻቸው የአገልግሎት መስጫ ማዕከል እና ሌሎች ቴክኒካል ጉዳዩች ጋር የተያያዙ ሃሳቦችን ምላሽ በሚሹት ጎራ አንስተዋል፡፡

ለተነሱ ሃሳቦች ተቋማዊ ምላሽ የሰጡት የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መስረት መስቀሌ በማጠቃለያቸዉ የመድረኩ ተሳታፊ ባንኮች እና ኢንሹራንሶች ትስስር ለመፍጠር ላሳዩት ፈቃደኝነት ልባዊ ምስጋናቸውን በመቸር በቀጣይ የስራ ውል ስምምነት በመፈራረም ወደ ትግበራ የሚገባ እና ፈጥነው ተግባራዊ የሚያደርጉ ባንኮችን እውቅና በመስጠት በሚዲያ ጭምር ለህዝብ ተደራሽ የሚሆንበት አሰራር እንደሚኖር አስታውሰው ፈጥኖ መተግበር ያለበት ጉዳይ በመሆኑ ባለስልጣኑ ባለሙያ በመመደብ በስፍራው አልያም በማዕከል ደረጃ ስልጠና ሰጥቶ በአጭር ቀናት ውስጥ ወደ ትግበራ እንደሚያስገባ እና ክትትል እና ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም በአሰራሩ ከ2018 በጀት ዓመት ጀምሮ የማንዋል መረጃ የማንቀበል በመሆኑ ማንኛውም ግዥ ፈጻሚ መ/ቤት የማንዋል ዋስትናን የማይቀበልበት አሰራር ይዘረጋል ፣ በሂደትም አስገዳጅ ሆኖ ሲስተሙ ራሱ የሚዘጋበት ሂደትን በማካተት የሚተገበር በመሆኑ ይህንን ተገንዝበን ለተግባራዊነቱ ዝግጁ ልንሆን ይገባል በማለት የውይይቱን መርሃ-ግብር አጠናቅቀዋል፡፡

የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓት(e-GP) በደቡብ ምዕራብ ክልል ለመተግበር  ስምምነት ተደረገ።

(ግንቦት 18ቀን 2017 ዓ.ም) በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ፋይናንስ ቢሮ እና በመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን መካከል የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓትን በክልሉ በተመረጡ የመንግስት መስሪያ ቤቶች  ለመተግበር  ስምምነት ተደረገ፡፡

በአዲሰአበባ ኃይሌ ግራንድ ሆቴል በተዘጋጀው የፊርማ ስነ-ስርዓት ላይ የተገኙት የፌዴራል የመንግስት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሠረት መስቀሌ የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓት በሁሉም የፌዴራል መ/ቤቶችና ቅርንጫፎቻቸው እየተተገበረ መሆኑን አንስተዉ  ስርዓቱን መተግበር ግልጽነትና ተጠያቂነትን በማስፈን፣ ብልሹ አሠራርን በማስወገድ፣ በመንግስትና በህዝብ መካከል መተማመን እንዲኖር ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማድረግ፤ በፋይናንስ አሰራር ላይ የሚነሱ ቅሬታዎች ለማስወገድ እንደሚያስችል ገልጸዋል።

አያይዘዉም የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓትን በፌደራል ብቻ ሳይሆን በሌሎች ክልሎች ለመተግበር እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል በራስ ተነሳሽነት ተቀብሎ ለመተግበር  መዘጋጀቱ የዘመነ የፋይናንስ አሰራር ለመከተል ያለዉን ከፍተኛ ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል።

በክልሉ ይህን ተግባራዊ ለማድረግ እንዲቻል ከ2018ዓም በጀት ዓመት ጀምሮ ለተመረጡ ቢሮዎች ባለሞያወች በባለሥልጣን መ/ቤቱ በኩል ስልጠናዎችና ሌሎች አስፈላጊ ቴክኒካል ድጋፎች እንደሚደረግላቸዉ ገልፀዋል፡፡

የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊዋ ክብርት ወሠነች ቶማስ እንዳሉት፤ የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት በክልሉ ግዥ በሚፈጽሙ በተመረጡ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የሚተገበር መሆኑን አስታውሰው ስርዓቱ የሚባክኑ ሀብቶች ለማዳን የሚያስችል ምቹ መደላድል የሚፈጥር መሆኑን አንስተው፤ የፋይናንስ ግልጸኝነትና ተጠያቂነትን በማስፈን በህዝብና መንግስት መካከል መተማመን እንደሚያጎልብት መገንዘባቸውን አስረድተዋል።

አክለውም በተለይም በመንግስት መስሪያ ቤቶች ከጨረታ ሂደት ጋር በተያያዘ ያለውን የወረቀት ንክኪ፣ የጊዜና የጉልበት እንዲሁም አለአግባብ የሚወጡ ወጪዎችን ማስቀረት የሚያስችል አሰራር መሆኑን ገልጸዋል።

አያይዘውም ክልሉ በቅርብ የተመሠረተ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በተለይም ከመሠረተ ልማት ጋር ተያይዞ ውስንነቶች እንደሚገጥሙ አንስተው ለአስቻይ ሁኔታዎች ከመስተዳድሩ ጋር በግልጽ መነጋገርና ለትግበራው በሙሉ ዝግጂነት መግባት እንደሚያስፈልግ ያላቸውን ዝግጁነት ገልጸው ባለስልጣኑ ወደ ሲስተሙ እንዲገቡ ለፈጠረላቸው መነቃቃት ምስጋናቸውን በማስቀደም ቀጣይም የተለመደ ድጋፍ እንደሚያደርግላቸው ያላቸውን ዕምነት ገልጸዋል።

አጠቃላይ ስለ ኢጅፒ ሲስተሙ ሙሉ ገለጻ እንዲሰጡ በስፍራዉ የተገኙትና ሲስተሙን ያለሙት የፔራጎ ኢንፎርሜሽን ኃ.የተ.ግ.ማ. የተሰኘው የሶፋትዌር ድርጅት ሃላፊ አቶ እውነቱ አበራ፤ ዘመናዊና ቀልጣፋ የፋይናንስ አሰራር መዘርጋት የሚያስችል ሶፋትዌር መሆኑን አንስተዉ፤ ይህም በመንግስት ግዥ የሚወዳደሩ ተቋማት ያለቦታ ገደብ እኩል በሆነ አሰራር ተጠቃሚ መሆን እንዲችሉ እንደሚያደርግ ተናግረዋል።
የግዥ ህግ በአግባቡ እንዲተገበር፣ የጊዜና ጉልበት ብክነት ከመቀነስ ባለፈ ከተለያዩ አማራጮች ጋር ተቀናጅቶ በመስራት ለጨረታና መሰል ግዥዎች ላይ የሚነሱ ቅሬታዎችን የሚያስቀር መሆኑን አመላክተዋል።

በመጨረሻም ሲስተሙን ለመጀመር ያለውን የተሻለ አማራጭና አስቻይ ሁኔታዎች የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር የገለጹ ሲሆን ክልሉ በአጭር ጊዜ ላሳየው ቁርጠኝነት ልባዊ ምስጋናቸውን በድጋሜ ችረዋል። ባለስልጣኑ ለየትኛውም ሙያዊ ድጋፍ ያለውን ዝግጁነትም አሳይተዋል።

በመጨረሻም ሲስተሙን ለመተግበር የሚያስችለውን የሥራ ስምምነት ሰነድ የክልሉ ፋይንናስ ቢሮ ከባለስልጣኑ ጋር ተፈራርሟል።

የፊደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን የባለስልጣኑን የዝግጅት ምዕራፍ የሪፎርም ስራዎችን ገመገመ፡፡

(ግንቦት19/2017ዓ/ም) በመንግስት አገልግሎት እና አስተዳደር ስርዓት ውስጥ በየዘርፉ የሚስተዋሉ የአሰራር ማነቆዎችን ነቅሶ በማውጣት ችግሮችን ደረጃ በደረጃ ለመፍታት የሚያስችለው ፖሊሲ ከመጽደቁ በተጫማሪ ከፖሊሲው የሚቀዳ የመንግስት አገልግሎት እና አስተዳደር የሪፎርም ስራ ተቀርጾ ወደ ትግበራ መገባቱ ይታወቃል፡፡

ሪፎርሙን በውጤታማነት ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የሪፎርም ትግባራ የሚመራበት አግባብ፣የትግበራ ምዕራፎችን እና የሚከናወኑ ተግባራትን በግልጽ የሚያመላክት እና አቅጣጫ የሚጠቁም ፍኖተ ካርታ ጭምር ተዘጋጅቶለት ለተግባራዊነቱ ወደ ተቋማት ወርዷል፡፡

ይህንን ሃገራዊ ተልዕኮ ለማስፈጸም ከተመረጡት ተቋማት መካከል አንዱ የሆነው የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የዝግጀት ምዕራፉን በተሻለ አፈጻጸም አጠናቋል፡፡ ይህን ተከትሎ በዛሬዉ ዕለት ትግበራዉን ለመደገፍ እና ለመቆጣጠር ኃላፊነት የተሰጠው የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ልዑኩን ለዚሁ የሪፎርም ስራዎች የዝግጀት መርሃ-ግብር ግምገማ በስፍራው አሰማርቷል፡፡

ልዑኩን ተቀብለው ያነጋገሩትና የተጠናቀቀዉን የዝግጅት ምዕራፍ የሪፎርም ስራዎች እንዲገመግም ተግባራቱን አደራጅተው የጠበቁት የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሠረት መስቀሌ በሪፎርም ስራዎች የተከናወኑ ተግባራትን አንድ በአንድ በሰነድ ማስረጃዎች ጭምር በማስደገፍ በገለጻቸውን አቅርበዋል፡፡

በዝግጅት ምዕራፍ ከተተገበሩት የሪፎርም ስራዎች ውስጥ በዋናነት የተቋሙን ዌብሳይት፣ የe-learning የመማሪያ ስርዓት፣ዘመናዊ የደብዳቤ ልዉዉጥ ስርዓት( Letter management system)በራስ አቅም አልምቶ መተግበሩ፣የነዳጅ አጠቃቀምና የተሸከርካሪ ስምሪት (e-fleet management)፣እየተዘጋጁና እየተተተገበሩ የሚገኙ መመሪያዎች፣አዋጁን አካታች ለማድረግ በምልክት ቋንቋ እና በብሬል ጭምር በማሳተም የተሰሩ ተግባራት፣ ለሴቶች እና ህጻናት እንዲሁም ለአካል ጉዳተኞች ልዩ ትኩረት በመስጠት የተተገበሩ ምቹ የስራ አካባቢን የመፍጠር ትግበራዎች፣ የe-GP ሲስተምን ተጠቃሚ ተቋማት የማስፋት እና የሲስተም ማሻሻያዎችን የማከናዎን ተግባራት፤የሲስተም ትስሰር ከሌሎች ተቋማት ጋር መፈጠሩ፤ተገልጋዩች ባሉበት ሆነው እገዛ የማግኘት፤ቅሬታ የማቅረብ እና ምላሽ የመቀበል አሰራርን ያካተተ የሲስተም ማሻሻያ ትግበራ መዘርጋቱ፣የተገልጋዩች ቻርተር መዘጋጀቱ፣ ልዩ ልዩ የአቅም ግንባታና ሙያዊ ስልጠናዎችን እንዲሁም ሌሎች ሰፊ የሪፎረም ስራዎች መከናወናቸውን በገለጻቸው አካትተዉ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ የሠነድ ማረጋገጫ ጭምር በማቅረብ አሳይተዋል፡፡

ልዑኩ በቀረበው ገለጻ ላይ ተመርኩዞ በተግባር ማየት የሚፈልጋቸውን ሁሉም ሰነዶች ቀርበውለት የተመለከተና በተጨባጭ መተግበሩን ጭምር ለማረጋገጥ ተዘዋሮ በመጎብኘት ያረጋገጠ ከመሆኑም ባሻገር በአፈጻጸሙ እጅግ ደስተኞች መሆናቸውን በማስቀደም፤ በተለይም ለሰራተኞች ምቹ የሥራ አካባቢን ለመፍጠር የተሄደበት እርቀት እና አገልግሎት አሰጣጡን ከማዘምን ጋር የተያያዙት ትግበራዎች ልዑኩ ከተሰማራበትና ልዩ ትኩረቱን አድርጎ ከሚገመግመበት አጀንዳዎች ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለዉ ጥሩ አፈጻጸም መሆኑን አበክረዉ ገልጸዋል፡፡

በመቀጠልም በልዩነት ሴት ሰራተኞችን ለመደገፍ እና ለማብቃት እየተከናወነ ያለው ቁልፍ ተግባር፣ ሠራተኞች ያለችግር ልጆቻቸው እየተከታተሉ እንዲሰሩ የተዘጋጀው የህጻናት ማቆያ፣ አዋጁን አካታች ለማድረግ የተሄደበት እርቀት (ብሬልን እና የምልክት ቋንቋን መጠቀሙ)፤ድህረ-ገጽ እና የe-learning ፕላትፎርም በራስ አቅም አልምቶ ወደ ተግባር መገባቱ እና አሰራርን በተለይም የግዥን ስርዓቱን ለማዘመን የተፈጸሙ ተግባራት ይበል የሚያሰኝ እና ለሌሎች ተቋማት ጭምር ለማሳያነት ሊውል የሚችል መልካም አፈጻጸም የታየበት ድንቅ ተግባር ነው ሲሉ አድናቆታቸውን ገልጸዋል። ልዑኩ በተገኘበት ወቅት የገንዘብ ሚኒስቴር ልዑክም እንደ ተጠሪ ለመደገፍና ለመከታተል በስፍራው ተገኝቷል።

በመጨረሻም የተከናወኑ ተግባራትን ተጨባጭነት ለማረጋገጥ የህጻናት ማቆያዉን ጨምሮ ሁሉንም የስራ ክፍሎች ተዟዙረዉ ጎብኝተው የግምገማ መረሃ-ግብሩ ፋጻሜውን አግኝቷል፡፡

ከሕዝብ ተወካዩች ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ እና ከፌደራል ዋና ኦዲተር ኃላፊዎች ጋር በነበረው የውይይት መድረክ የተነሱ ዋና ዋና ጥያቄዎች፤ሃሣብ እና አስተያየቶች ከተሰጡ ማጠቃለያዎች ጋር

(ግንቦት20/2017ዓ/ም) ከቀረበው ሰፊ ገለጻ በኋላ በሁለቱም ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዎች እና አባላት እንዲሁም የፌደራል ዋና ኦዲተር የስራ ኃላፊዎች ግልጽነት የሚሹ ጥያቄዎች እና ሃሳብ አስተያየቶች ተነስተዋል፡፡

ዕድሉን የወሰዱ ተሳታፊዎች የኢጂፒ ሲስተም በሁሉም የፌደራል ተቋማት እና በ93 ቅርንጫፎቻቸው ከመስፋፋቱም ባለፈ ለሌሎች የአፍሪካ ሃገራት ጭምር ለተሞክሮ ማጋሪያነት መዋሉ፣ሪፎርሙን ከአዋጅ ጋር አስተሳስሮ መተግበሩ፣ አዋጅ ቁጥር (1333/2016) ለማስተግበር የሚያስችሉ የተለያዩ መመሪያዎችን ለማዘጋጀት የተደረገው ጥረት፣ የአዋጁን አካታችነት እና ተደራሽነት ለማሳለጥ በምልክት ቋንቋና በብሬል ጭምር መታተሙ፣ በአመራሮች እና ባለሙያዎች ላይ የነበረው ቁርጠኝነት፣ በመርህ ደረጃ የሚወሩ ህጎችን በተግባር ለማሳየት የተደረገው ጥረት እና መሠል ጉዳዮች በአዎንታዊነት ከተነሱት መካከል ይገኙበታል፡፡

ከሲስተሙ ጋር ተያይዞ ከደህንነት ፖሊሲ፣ነጋዴው ማህበረሰብ ሲስተሙን መጠቀም እንዲችል ግንዛቤ ከማሳደግ ጋር በተያያዘ፣ የተጠቃሚዎች የእርካታ ዳሰሳ ከመተግበሩ ጋር የተያያዙ፣ ከሲስተም ትስሰር እና ቴክኖሎጂውን ከሚያስተዳድር የስራ ክፍል ጋር የተያያዘ እና መሰል ጉዳዩች ግልጽነትት ከሚሹት ጎራ ተነስተዋል፡፡

ከአጠቃላይ የተቋሙ የስራ እንቅስቃሴና አዲሱ አዋጅ ጋር በማስተሳሰር ከተነሱት መካከል ደግሞ አዋጁን ለማስፈጸም የሚዘጋጁ መመሪያዎች መዘግየት፤ የደንብ አለመወጣት፣ የሚያስፈልጉ ማሻሻያዎችን አጥንቶ ከማቅረብ አኳያ እና መሰል ተያያዥ ጉዳዩች ምላሽ ከሚሹት መካከል ይገኙበታል፡፡

በመቀጠልም የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ መሠረት መስቀሌ የመድረኩ ዋና ዓላማ እየሰራን ያለውን ገልጸን የሚሰጡ ሃሳቦችን ወስዶ ለማሻሻል ስለሆነ የተነሱ ሃሳቦችን በግብዓትነት የምንወስድ ሲሆን በቀጣይ ወደ ዕቅድ በመቀየር ተግባራዊ እናደርጋቸዋለን ብለዋል፡፡

አያይዘውም የተሰጡ አዎንታዊ አስተያየቶች በሙሉ ውጤታቸው የተመዘገበው በአመራሩ ቁርጠኝነት ብቻ ሳይሆን ሲስተም ካለማው አካል ጀምሮ ባለሙያዎች በኃላፊነት ስሜት ያከናወኗቸው ተግባራት የጋራ ድምር ዉጤት በመሆኑ አድናቆቱ ለሁሉም ይድረስ ሲሉ ተሰምተዋል፡፡

አያይዘዉም ለተነሱ ሀሳብ አስተያየቶች ጥቅል ተቋማዊ ምላሽ የሰጡ ሲሆን በተለይም ኢጂፒ ሲሰተም ሙሉ በሙሉ ሊያስገኝ የሚገባው ጥቅም እንዲስያገኝ ከማድረግ አኳያ፣ተቋማት የግዥ ስራዎችን ከሲስተሙ ጋር አስተሳስረው እንዴት እየተገበሩ እንዳለ የመደገፍ ሂደት ላይ፣ከሲስተሙ ደህንነት ፣ለንግዱ ማሀበረሰብ ሊሰጥ ከሚገባዉ ግንዘቤ የማሰጨበጥ ተግባር፣አዋጁ መመሪያ እንዲወጣላቸው በሚፈቅድላቸው ጉዳዩች ላይ መመሪያዎችን በማውጣት ረገድ፣ የባለስልጣኑን ድጋፍ በሚሹ በሁሉም ተቋማዊ ጉዳዮች፣የፌደራል ቅርንጫፍ መ/ቤቶችንና ክልሎችን ወደ ሲስተሙ በማስገባት ረገድ እና መሰል ተግባራት ላይ ቅድሚያ ተሰጥቶት በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም በህዝብ ተወካዩች ም/ቤት የፕላንና ልማት እና ፋይናስ ጉዳዩች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሰቢ አቶ ደሳለኝ ወዳጆ በማጠቃለያ ንግግራቸው ምክር ቤቱ አዋጁን ከማዘጋጀት እና ከማጽደቅ ባሻገር የመከታተል እና መተግበሩን የማረጋገጥ ድርሻ ያለው መሆኑን አስታውሰው ጸድቆ ወደ ተግባር በተለወጠው አዋጅ ደስተኞችና እንደ ሃገርም ተጠቃሚ ሆነናል ብለዋል፡፡

አክለውም ከአዋጁ መጽደቅ በኋላ ትግበራውን የማወቅ ፍላጎት እንደነበራቸዉ ገልጸዉ በዚህ የውይይት መድረክ ያለበት የትግበራ ሂደት ይበልጥ ግልጽ የሆነላቸዉ መሆኑን በማሰቀደም ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል በሚሉት ሁሉም ጉዳዩች የግዥዉ ዘርፍ የሃገሪቱን ከፍተኛ በጀት የሚይዝ እንደመሆኑ መጠን ትልቁን ሃላፊነትና የማስፈጸም ድርሻ የተሰጠዉ ባለስልጣኑ ዘመናዊ አሰራርን በሃገራችን ተግባራዊ ከማድረግ ባለፈ ዓለምአቀፍ የገበያ ትስስር እንዲፈጠር በማድረግ ረገድ ሊተጋ ይገባል ሲሉ ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም ለተሻለ ለዉጥና ተጠቃሚነት በሚያስፈልጉ ማሻሻያዎች ዙሪያ ጥናት በማድረግ ቢመጣ በም/ቤቱ በኩል ማሻሻል የሚቻልበት አግባብ መኖሩን በመጠቆም የዉይይት መርሃ- ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል።