The FDRE Public Procurement and Property Authority

በኢፌዲሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን

ለሙከራ ትግበራ በተመረጡ ዘጠኝ(9) የፌዴራል ተቋማት ከሐምሌ 1/2013 ዓ.ም ጀምሮ የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ (e-GP) ተግባራዊ እንደሚሆን ተገለፀ

አዲሱን የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ተግባራዊነት አስመልክቶ ለመድሃኒትና ኬሚካል አስመጭዎችና ወኪሎች፣ በኮንስትራክሽን ዘርፍ ለተሰማሩ ኮንትራክተሮች ና ማህበራት እንዲሁም ሌሎች ልዩ ልዩ ቁሳቁሶችን ለሚያስመጡ አቅራቢዎች፣ ለዘርፍ ማህበራት ምክርቤቶችና ድርጅቶች ገለጻ የተደረገ ሲሆን የፌዴራል የመንግስት ግዥና ንብረት አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀጂ ኢብሳ ለሙከራ ትግበራ በተመረጡ ዘጠኝ የፌዴራል ተቋማት የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ከሐምሌ 1/2013 ዓ.ም ጅምሮ ተግባራዊ እንደሚደረግ ገልፀዋል፡፡

የሙከራ ተግበራ የሚደረግባቸው ተቋማት የገንዘብ ሚኒስቴር፣ የገቢዎች ሚኒስቴር፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን፣ የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ ኤጀንሲ፣ የመንግስት ግዥና ንብረት ማስወገድ አገልግሎት፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ፣ የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ እንዲሁም ኤጀንሲው መሆኑን ጠቁመው በነኝህ ተቋማት የሚወጡ ጨረታዎች ሙሉ በሙሉ በሲስተሙ ተግባራዊ ይሆናል ያሉ ሲሆን ከስድስት ወራት በኋላ 50 የፌዴራል ተቋማት በሲስተሙ የሚካተቱ ሲሆን በአጭር ጊዜ ሁሉም የፌዴራል ተቋማት በሲስተሙ የሚታቀፉ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

አለም አቀፍ ተሞክሮ እንደሚያሳየው የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ የተጠቀሙ ሀገራት ከ5-25% ከበጀታቸው መቆጠብ ችለዋል፡፡ አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያመላክቱት ከ60-70% የሚሆነው የሀገራችን የመንግስት በጀት ለግዥ ይውላል ያሉ ሲሆን ዋና ዳይሬክተሩ አዲሱን የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ተግባራዊ በሚደረግበት ወቅት 1% ከመንግስት በጀት ወጭ መቆጠብ ከተቻለ በ2014 የበጀት ዓመት ከተመደበው በጀት ከ3 ቢሊየን ብር በላይ ወጭ መቀነስ ያስችላል ብለዋል፡፡

ተሳታፊዎች በበኩላቸው ዘርፉ በኤሌክትሮኒ ሲስተም መደገፉን አድንቀው ከስራዎች ክብደት፣ ከአቅም ግንባታ፣ ከባለሙያ ፍልሰት፣ ከኔትወርክ መቆራረጥ፣ ከክህሎት ክፍተት አንፃር ችግር ሊገጥማቸው እንደሚችል ጠቁመው በተለይ በመድሃኒትና ኬሚካል አስመጭነት ከአለም ዓቀፍ የመድሃኒት አምራቾች ጋር በውክልና የተሰማሩ አቅራቢዎች ሲስተሙ ከገበያ ሊያስወጣን ይችላል ብለዋል፡፡

ከተሳታፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎች የኤጀንሲው ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ወልደአብ ደምሴ ምላሽ የሰጡ ሲሆን የአቅራቢዎችን የአቅም ግንባታ ክፍተት ለመሙላት ስልጠናና ልዩ ልዩ የአቅም ማጎልበቻ ዘዴዎች በቀጣይ እንደሚዘጋጁ ጠቁመው አዲሱ የመንግስት የኤሌክትሮኒክ የግዥ ስርዓት በማንዋል ሲደረግ የነበረውን የግዥ ስርዓት ወደ ኤሌክትሮኒክ ከመቀየር በስተቀር አዲስ ህግ አለመውጣቱን ገልፀው በነባሩ ህግ ሲከናወኑ የነበሩ አሰራሮች በሲስተሙ የሚቀጥሉ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ከኔትወርክና ከሃይል መቆራረጥ ጋር ተያይዞ ለሚፈጠሩ ችግሮች ኤጀንሲው የመፍትሔ አቅጣጫዎችን እንደሚያስቀምጥ ገልጸዋል፡፡

ለሲስተሙ ስኬታማነት የአቅራቢዎች ተሳትፎ እጅጉን ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው አቅራቢዎች ከሐምሌ 1/2013 ዓ.ም ጀምሮ ምዝገባ በማከናወንና የነቃ ተሳትፎ ማድረግ እንደሚገባቸው ም/ዋና ዳይሬክተሩ ጨምረው ገልፀዋል፡፡

ለተሳታፊዎች አቶ ታደሰ ከበደ የመንግስት ግዥና ንብረት አስተዳደር ኤጀንሲ የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ፕሮጀክት የግዥ ስፔሻሊስት እንዲሁም ሶፍትዌሩን ያለሙት አቶ እውነቱ አበራ የፔራጎ ኢንፎርሜሽን ሲስተም ሶማኔጅንግ ዳይሬክተር ፅሁፋቸውን አቅርበዋል፡፡