The FDRE Public Procurement and Property Authority

በኢፌዲሪ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን

News

በአቅራቢነት ስለመመዝገብ

በባለስልጣኑ አዲሱ ዌብ ፖርታል ላይ በአቅራቢነት በቀላሉ ለመመዝገብና ጨረታዎችን በኦንላይን ለመሳተፍ ይረዳ ዘንድ የተዘጋጀውን የአጠቃቀም ማኑዋል (User Guide for Supplier) የሚለውን በቅድሚያ በመመልከት ይመዝገቡ፡፡

eGP- easy. efficient. secure

በግንባታ ግዥ፣በምክር አገልግሎት ግዥ፣በውል አስተዳደር እና በንብረት አስተዳደርና አወጋገድ ዙሪያ ሥልጠና ተሰጠ

የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን በሀገራችን ከሁሉም ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት (ከትግራይ ክልል ውስጥ ካሉ ዩኒቨርሲቲዎች ዉጪ) ጉዳዩ የሚመለከታቸው የግዥ እና ንብረት አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች እንዲሁም የግዥ አፅዳቂ ኮሚቴዎች የተሳተፉበት በዩኒቨርሲቲዎች አከባቢ የሚታዩ የግንባታ ግዥ፣የምክር አገልግሎት ግዥ፣ውል አስተዳደር እና በንብረት አስተዳደርና አወጋገድ ዙሪያ ከነሐሴ 4 እስከ 7 ቀን 2014 ዓ.ም ባሉት ተከታታይ ቀናት በሶስት ክላስተሮች በመከፋፈል በአርባ-ምንጭ፣ በደብረ-ማርቆስ እና በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመተባበር የአቅም ግንባታ ሥልጠና ተሰጠ፡፡
የአቅም ግንባታ ሥልጠው ዋና ዓላማ ግልፅ፣ ዘመናዊ ቀልጣፋና ውጤታማ የመንግስት ግዥ አፈፃፀምና ንብረት አስተዳደር ማስፈን፣ የመንግስትን ንብረት በጥንቃቄ የመያዝ፣ የመጠቀምና የመቆጣጠር እንዲሁም ንብረቱ አገልግሎቱ ሲያበቃ በወቅቱና በተገቢው መንገድ እንዲወገድ ማስቻል ነው፡፡
የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ትዉልድን በመቅረፅ ከሚያደርጉት ጎን ለጎን በግዥ አፈፃጸም ተግዳሮቶች፣ በልዩ ግዥ ፍላጎት መበራከት፣ በአቤቱታ እና ጥፋተኝነት ጉዳዮች መብዛት እና በግዥ አፈፃፀም ዙሪያ የሚታዩ የኦዲት ግኝቶች፣ የግንባታ ፕሮጀክቶች የጨረታ ሂደት ዙሪያ የሚታዩ ተግዳሮቶችና የመፍትሄ አቅጣጫዎቻቸዉ እንዲሁም በአጠቃላይ በግዥ ዙሪያ የሚታዩ የግብዓት ጥራት ችግሮችና መፍትሄዎቻቸው እና ሌሎች የአሰራር ግድፈቶችን በመቅረፍ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ለማስቻል ነው፡፡
መንግስት ከመንገድ ግንባታ ቀጥሎ ከፍተኛ በጀት የሚመድብ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በመሆኑ፤ ዩኒቨርሲቲዎች የሚያንቀሳቅሱት በጀት ከፍተኛ በመሆኑ በየተቋማቶቹ የሚገኙ የግዥ ባለሙያዎችና የስራ ኃላፊዎች በግዥ ዘርፍ የአስተሳሰብ ለውጥ በማምጣት ገንዘብ ሊያስገኝ የሚችለውን ጥቅም ማስገኘት የሚገባቸው መሆኑን የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የሥራ ኃላፊዎች ስልጠናውን በከፈቱበት ወቅት ተናግረዋል፡፡
በባለስልጣኑ በኩል ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የስራ ኃላፊዎችም ሆነ ለባለሙያዎች ተደጋጋሚ በግዥና ንብረት ዙሪያ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎችን የሚሰጥ ሲሆን የሚሰጡ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች የባህሪይ ለውጥ በማምጣት በተለይ በዩኒቨርሲቲዎች እየታየ ያለው የኦዲት ክፍተት በአግባቡ መታየትና መሻሻል ይገባዋል ብለዋል፡፡
በቀጣይ ሁሉም የሀገራችን ዩኒቨርሲቲዎች ጥራት ያለው ትምህርት ለመስጠት ብሎም ምርምር ለማካሄድ ግዥ የጀርባ አጥንት በመሆኑ፤ የሚገዙ ግዥዎችን በጊዜና በጥራት መግዛት እንደሚገባ እንዲሁም ህግና ስርዓትን የጠበቀ የግዥና የንብረት አስተዳደር ማስፈን እንደሚጠበቅባቸው ገልፀዋል፡፡
በሶስቱም የክላስተር የተሰጠው የአቅም ግንባታ ሥልጠና ላይ ከ600 በላይ የግዥና ንብረት ባለሙያዎችና ኃላፊዎች ተሳትፈዋል፡፡


ከመንግሥት ግዥ አፈጻጸም ጋር በተያያዘ የሚስተዋል ሌብነትን የሚያስወግድ አሠራር እየተዘረጋ ነው

"ከመንግሥት ግዥ አፈጻጸም ጋር በተያያዘ የሚስተዋል ሌብነትን የሚያስወግድ አሠራር እየተዘረጋ ነው" የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሀጂ ኢብሳ
ባሕር ዳር: ሐምሌ 24/2014 ዓ.ም (አሚኮ) ከሀገሪቱ ትልልቅ ፕሮጀክቶች እሰከ የመንግሥት ተቋማት የሚስተዋለው ውስብስብ ሌብነትና ብልሹ አሠራር እያደረሰ ያለው  ኪሳራ ሀገርን ዋጋ እያስከፈለ እንደኾነ ይነገራል። "የሰለጠነ፣ ስብዕናው የተገራ፣ የችግር መፍቻ ቁልፍ ማዕከል ነው "ተብሎ በሚታመንበት የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሳይቀር ከግዥና ንብረት አስተዳደር ጋር በተያያዘ የሚስተዋሉ ብልሹ አሠራሮች መኖራቸው ደግሞ ጉዳዩን አሳሳቢ ያደርገዋል።
የኢፊዴሪ የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሀጂ ኢብሳ እንደሚሉት ከጠቅላላው የሀገሪቱ ዓመታዊ በጀት ከ65 በመቶ በላይ የሚኾነው ገንዘብ ለግዥ ይውላል። ይኽ ከፍተኛ መዋለንዋይ የሚፈስበት ዘርፍ በሌብነትና በብልሹ አሠራር መተብተቡ  ሀገርን ዋጋ እያስከፈለ ነው። ፕሮጀክቶች በታቀደላቸው ጊዜ አለመጠናቀቅ ከግዥና ከጫራታ ጋር በተያያዘ የሚፈጠር መስተጓጎል ዋነኛው ምክንያት ነው የሚሉት ዋና ዳይሬክተሩ በአንድ ወቅት በሀገሪቱ የሚገነቡ የመንግሥት ፕሮጀክቶች  በታቀደላቸው ጊዜ ባለመጠናቀቃቸው ምክንያት ብቻ  እስከ 43 ቢሊየን ብር ተጨማሪ በጀት ጠይቀዋል ነው ያሉት።  በሀገሪቱ ለግዥ ከፍተኛ  በጀት ከሚበጀትላቸው ተቋማት ዩኒቨርሲቲዎች ቀዳሚ መኾናቸውን የሚናገሩት ዋና ዳይሬክተሩ ከግዥና ሃብት አስተዳደር ላይ የሚስተዋልባቸውን ብልሹ አሠራር ለመቅረፍ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው ብለዋል።  የአሠራርና የእውቀት ክፍተቶችን በመሙላት፣ ኾን ተብሎ የተፈጠረን ብልሹ አሠራር ላይ ደግሞ ሕጋዊ እርምጃ እየተወሰደ መኾኑን ነው የተናገሩት።
በፌዴራል ደረጃ ብቻ 450 ተቋማት ላይ ከግዥ ሥርዓት ጋር በተያያዘ በተፈጠረ ሕገወጥ ድርጊት እርምጃ ተወስዷልም ነው ያሉት።  ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ባላቸው የግዥና ንብረት አስተዳደር ጥራት ወስብስብ ችግር ያለባቸውን "ቀይ"፣ መጠነኛ ቸግር ያለባቸውን "ቢጫ"፣ጥሩ አሠራር ላይ ያሉትን ደግሞ "አረንጓዴ" እያሉ ደረጃ በመስጠት ከችግራቸው እንዲላቀቁ የግንዛቤ ሥራ ተሠርቷል ነው ያሉት።  በዚህም በተደጋጋሚ በተደረገ ስልጠናና የማስተካከያ እርምጃ አንዳንድ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ከቀይ ወደ አርንጓዴ መሸጋገር መቻላቸውን አንስተዋል።
"አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ፣አርሲና ድሬዳዋ ዩኒቨርስቲዎችን  ከቀይ ወደ አረንጓዴ የተሸጋገሩ" ሲሉም በምሳሌነት ጠቅሰዋል።  በመንግሥት የግዥ ሥርዓት ከጨረታ እሰከ የሚገዛው እቃ የጥራት ችግር ሀገርን ኪሳራ ላይ የሚጥሉ ውስብስብ ችግሮች አሉ የሚሉት ዋና ዳይሬክተሩ በተላይም ከተጫራች ጋር መደራደር፣ጨረታን ማዘግየት፣ከሕግ ውጭ ውስን ተጫራቾችን ብቻ ማሳተፍ፣የጨረታ ሰነድ አልቋል ማለት እና ሌሎችም ሕገወጥ ድርጊቶች የመንግሥት ሃብትና ንብረት በብልሹ አሠራር እየተዘረፈ ነው ብለዋል።
የመንግሥትን የግዥ ሥርዓት የመዘረጋትና  የመቆጣጠር ስልጣን የተሰጠው የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለስልጣን መስሪያቤትም ሕገወጥነትን ለመከላከል  ተቋማት የሚያወጡት ጨረታ በኤሌክትሮኒክስ ግብይት ሥርዓት እንዲኾን የሚያስገድድ አሠራር ዘርግቷል ብለዋል።  ይህ ሥርዓት የሚፈጠርን ሌብነትና ብልሹ አሠራር የሚቀርፍ ይኾናል የሚሉት ዋና ዳይሬክተሩ በቅርቡ 115 የመንግሥት ተቋማት ወደ ኤሌክትሮኒክስ ግብይት ሲስተም ይገባሉ ብለዋል።  የሚጀመሩ ፕሮጀክቶች በታሰበላቸው ጊዜና በጥራት እንዲጠናቀቁ የሚወጡ ጨረታዎች ሥራ ተኮር እንጂ ሰው ተኮር እንዳይኾኑ
ስለሀገሩ የሚጨነቅ ፣ ሀገሩን የሚወድና ስብዕናው የተገነባ ዜጋ መፍጠር ይገባል የሚሉት ዋና ዳይሬክተሩ የአሠራር ሥርዓትን ከመዘርጋት ባሻገርም የአሠራር ግድፈትን ለመቅረፍ ስልጠናና ግንዛቤ ፈጠራ ላይ እየተሠራ ነው ብለዋል።  ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋርም የጋራ ፎረሞችን እያዘጋጁ ምርምርም ምክክርም እየተደረገ መኾኑን ነው የተናገሩት።


ባለስልጣኑ ከክልል አቻ የግዥና ንብረት ተቆጣጣሪ አካላት ጋር ተወያዬ

የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ከክልል አቻ የግዥና ንብረት ተቆጣጣሪ ተቋም እንዲሁም የማዕከል ግዥ ፈፃሚ አካላት ጋር በባህርዳር ከተማ የምክክር መድረክ እያከናወነ ይገኛል፡፡
የምክክር መድረኩ ከሐምሌ 25 ቀን 2014 ዓ.ም ጀምሮ ለሶስት ቀናት የሚቆይ ሲሆን ከሁሉም ክልሎች (ከትግራይ ክልል በስተቀር) የተውጣጡ የግዥ ተቆጣጣሪነት ሚና ያላቸው ተቋማት እና ሌሎች ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡
በምክክር መድረኩ የክልሎች የቁልፍ ግዥ አፈፃፀምና ተሞክሮ፣ የክልሎች ተቆጣጣሪ አካላት የወረዳ ግዥ ኦዲትና የካልም (CALM) ወረዳዎች ኦዲት አፈፃፀም ሪፖርትና ተሞክሮ፣ በማዕቀፍ ግዥ አላማና መርህ፣ የመንግስት ግዥ አገልግሎት ሰጭ አካላት ኃላፊነትና ሚና፣ የመንግስት ግዥ አፈፃፀም እና የንብረት አወጋገድና ተሞክሮ የሚቀርብ ሲሆን በተጨማሪም ከዓለም ባንክ በተጋባዥ እንግዶች የMethodology for Assessment of Procurement System-II (MAPS-II) ሪፖርትና ዋና ዋና ችግሮች ቀርበው፤ የMAPS-II ውጤት ይፋ ማድረግ ስራ ይሰራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ባለስልጣኑ ከክልል አቻ የግዥና ንብረት ተቆጣጣሪ ተቋም እንዲሁም የማዕከል ግዥ ፈፃሚ አካላት ጋር ከሚያከናውነው ምክክር መድረክ የልምድ ልውውጥ ከመደረጉም ባለፈ ጥሩ ግብአቶች ይገኙበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የመንግሥት በጀት ውስን ነው። ይሄ ውስን ሀብት የሚሰበሰበው ከእያንዳንዷ እናት መቀነት ተፈትቶ ከታክስና ግብር ነው። በመሆኑም በአግባቡ ሕግና ሥርዓትን ተከትሎ ለሀገር ልማትና ዕድገት መዋል እንዳለበት ይታመናል። በየመንግሥት መሥሪያ ቤቱ የሚመደበውን በጀትም በአግባቡ ሥራ ላይ ማዋል ይገባል።

የመንግሥት ግዢዎች ፣ ለግንባታ የሚወጣ ወጪ፣ ትላልቅና ትናንሽ ፕሮጀክቶች ግንባታ በሚካሄድበት ጊዜ ፣ ወጪና ጉልበት ቀናሽ በሆነ መልኩ ጥራታቸውን የጠበቁ መሆን አለባቸው። ሁሉም የሀገር ሀብት የሁሉም ዜጋ ሀብትና ንብረት ነውና ይሄንኑ ውስን ሀብት በአግባቡ ሥራ ላይ ማዋል ከሁሉም ዜጋ የሚጠበቅ ይሆናል።
ይሁን እንጂ አሁን ባለው ሁኔታ የመንግሥት ሀብትና ንብረት አለአግባብ ሲባክን ይታያል። በእውቀት ማነስ ፣ በቸልተኝነት፣ ወይም ደግሞ ወደ ግለሰቦች ኪስ እንዲገባ ታስቦና ታቅዶ የገንዘብ ብክነት ሲፈጸም ይስተዋላል። ይህን የሚመለከት ሠራተኛ፣ ተቆጣጣሪ እና ኃላፊ ብልሹ የሆነ አሠራር ሲኖር ሕግና ሥርዓት እንዲይዝ ማድረግ ፤ ከዚህም አለፍ ብሎ እርምጃ እንዲወሰድ ጭምር መሥራት አለበት ። ነገር ግን አሁን በሚታየው ሁኔታ የሚባክነው የመንግሥት ሀብት እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ እንዳልሆነ ከፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የሚገኙ መረጃዎች ያመላክታሉ።
የዚህም ዋና ምክንያት ተደርጎ የሚጠቀሰው የመንግሥት መሥሪያ ቤት አሠራርን ያለማወቅና ከብቃት እንዲሁም ክህሎት ማነስ ጋር ተያይዞ ነው። የመንግሥት የአሠራር ሥርዓትን ባለመከተል፣ በቸልተኝነት እና በድፍረት እየተፈጸመ ያለ የአሠራርና የሕግ ጥሰቶች በመኖራቸው ምክንያት ነው ፡፡
በመሆኑም ለተቋማት የሚመደብ በጀት ፤ ለፕሮጀክቶች የሚመደብ ገንዘብ በአግባቡና በወቅቱ ለታለመለት ዓላማ እንዲውል ማድረግ ይገባል። ለዚህም የቅርብ ክትትልና ቁጥጥር ማድረግ በአጥፊዎች ላይም አስተማሪ ቅጣት መውሰድ ያስፈልጋል። ብልሹ አሠራርን በማጋለጡ ሂደት በተለይ ደግሞ የውስጥ እና የውጪ ኦዲተሮች ትልቅ ኃላፊነትና የሕዝብ አደራ አለባቸው። የእያንዳንዱን ተቋም የፋይናንስ ሥርዓት በመመርመር ሪፖርት ማድረግ፣ ብልሹ የሆኑ አሠራሮችንም ማጋለጥና ለነገ ትምህርት እንዲወሰድባቸው ማድረግ ይገባቸዋል ።
ከዋና ኦዲተር ባገኘነው መረጃ መሠረት፤ አሁን ባለው ሁኔታ የመንግሥት ተቋማት ያለአግባብ ወጪ ሂሳብ ግኝቶች እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ አይደለም። የተሟላ የወጪ ማስረጃ ሳይቀርብ በወጪ የሚመዘገብ ሒሳብ፣ ደንብና መመሪያን ሳይከተሉ ግዥዎች መፈጸም ፣ ማስረጃ ሳይኖር በወጪ የተመዘገበና ትክክለኛነቱን ለማረጋገጥ የማይቻል የወጪ ሂሳብ ግድፈቶች የመሳሰሉት ተጠቃሽ ናቸው።
ከ2008 እስከ 2013 ዓ.ም ድረስ ያለውን በንጽጽር ሲታይ በ2008 ዓ.ም ያለአግባብ የወጣው ወጪ 826 ነጥብ 4 ሚሊዮን ብር ሲሆን ከስድስት ዓመት በኋላ አሁን ይሄ ቁጥር ወደ አራት ነጥብ ዘጠኝ ቢሊዮን ብር አሻቅቧል ፡፡ ይሄ ሲታይ ያለአግባብ የሚወጣው ወጪ እየጨመረ እንጂ እየቀነሰ አለመሆኑን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል ። ይህም የመንግሥት ሀብት በአግባቡ ለታለመለት ዓላማ እንዳልዋለ የሚያመላክት ነው። በመሆኑም ተቋማትን የሚመሩ አካላት በየጊዜው በኦዲቱ የሚሰጣቸውን የማሻሻያ ሃሳቦች መነሻ በማድረግ እርምጃዎችን ከስር ከስር መውሰድ አለባቸው።
አሁን እየታየ ያለው ከጊዜ ወደ ጊዜ ከመስተካከል ይልቅ የሕግ ጥሰቶች፣ የግዥ ሥርዓቱን ተከትሎ ያለመሄድ ሁኔታ እየጨመረ ነው። በመሆኑም የዋናው ኦዲተር መሥሪያ ቤት በየተቋማት ያሉትን ችግሮች በመለየትና የሂሳብ ግኝቶችን ወደ አደባባይ በማውጣት ጥሩ እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል። የፋይናንስ ሕግና ሥርዓትን ተከትለው የማይሠሩ ወይም ያልሠሩ ተቋማትን የኦዲት ሪፖርት ለፓርላማው ከነስማቸውና ጉድለታቸው በማቅረብ በአደባባይ ማጋለጥ ጀምሯል። ይሄ ይበል የሚያሰኝ ጅምር ነው ። ሆኖም ግን በቂ ነው ማለት አይደለም።

አሁንም ቀጣይ ሥራዎች መኖር አለባቸው። ከኦዲት ግኝት ሪፖርቱ በመነሳት ጉዳዩ የሚመለከተው አካልም መውሰድ የሚገባውን ሕጋዊ እርምጃ መውሰድ አለበት። በሕግ አግባብ መጠየቅ ያለበት አካል ካለም ሳይሸፋፈንና የስልጣን ደረጃው ሳይለይ በሕግ አግባብ ተጠያቂ መደረግ አለበት። ይሄም ልክ እንደ ኦዲት ሪፖርቱም ውጤቱ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲሁም ለሕዝቡ መግለጽ ያስፈልጋል።
መወሰድ በሚገባው ልክ እርምጃ ካልተወሰደም የኦዲት ግኝት መኖሩን ያሳወቀው ዋና ኦዲተር የሥራውን ውጤት ቢያቀርብም እርምጃ መውሰድ የሚገባው አካል ግን ኃላፊነቱን አልተወጣም ሲል የተቋማቱን ስም በግልጽ ለፓርላማው ማሳወቅ ይኖርበታል። የዚህ ጉዳይ አስፈላጊነት አንዱ ከሌላው እንዲማር ለማድረግ ነው። ስለዚህ በቀጣይ ዋናው ኦዲተር አሁን ካደረገው እርምጃ አለፍ ብሎም በዚህ ልክ ሥራቸውን ያልሠሩና ኃላፊነታቸውን ያልተወጡ ተቋማትና የሥራ ኃላፊዎችን ማጋለጥ ይገባዋል። የመንግሥትና የሕዝብ ገንዘብና ሀብት ለታለመለት ዓላማ እንዳይውል ያደረጉና ለግል ጥቅማቸው ያዋሉትንም ማጋለጡን አጠናክሮ መቀጠል አለበት! የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም ግኝቶቹን ተከትሎ አስተማሪ እርምጃ መውሰድና ማስተካከል ለነገ ይደር የማይባል ሥራ ሊሆን ይገባል!

በግዥ አፈጻጸምና ንብርት አስተዳደር ዙሪያ ውይይት ተካሄደ

የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን በሀገራችን ከሁሉም (ከትግራይ ክልል ዉጪ) ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች ጋር በግዥ አፈጻጸምና ንብርት አስተዳደር ዙሪያ በሚስተዋሉ ተግዳሮቶች፤ በወቅታዊ የገበያ ሁኔታ እና በመሳሰሉት ጉዳዮች ላይ ከሌሎች ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ሐምሌ 23 እና 24 ቀን 2014 ዓ.ም ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ለሶስተኛ ዙር የምክክር መድረክ እያካሄደ ይገኛል፡፡ የምክክር መድረኩ ዋና ዓላማ ግልፅ፣ ዘመናዊ ቀልጣፋና ውጤታማ የመንግስት ግዥ አፈፃፀምና ንብረት አስተዳደር ማስፈን፣ የመንግስትን ንብረት በጥንቃቄ የመያዝ፣ የመጠቀምና የመቆጣጠር እንዲሁም ንብረቱ አገልግሎቱ ሲያበቃ በወቅቱና በተገቢው መንገድ እንዲወገድ ማስቻል  ነው፡፡

የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ትዉልድን በመቅረፅ ከሚያደርጉት ጎን ለጎን በግዥ አፈፃጸም ተግዳሮቶች፣ በልዩ ግዥ ፍላጎት መበራከት፣ በአቤቱታ እና ጥፋተኝነት ጉዳዮች መብዛት እና በግዥ አፈፃፀም ዙሪያ የሚታዩ የኦዲት ግኝቶች፣ የግንባታ ፕሮጀክቶች የጨረታ ሂደት ዙሪያ የሚታዩ ተግዳሮቶችና የመፍትሄ አቅጣጫዎቻቸዉ እንዲሁም በአጠቃላይ በግዥ ዙሪያ የሚታዩ የግብዓት ጥራት ችግሮችና መፍትሄዎቻቸው እና ሌሎች የአሰራር ግድፈቶችን በመቅረፍ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ለማስቻል ነው፡፡  ከምክክር መደረኩ በግዥ አፈፃጸምና አጠቃላይ በንብረት አስተዳደር ዙሪያ የሚስተዋሉ ችግሮችን መቀነስ ዙሪያ ትልቅ አስተዋፅኦ ከሚኖረው ባሻገር በአገር ደረጃ ከ70% በላይ የሚሆነውን የመንግስት በጀት ውጤታማነትን ከማሳደግ አንፃርና የመንግስትን የግዥ አፈፃፀምና ንብረት አስተዳደርን ከብክነት ለማዳን ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት የሚደረግ ምክክር መድረክ በመሆኑ ባለሥልጣኑ ለሚያከናውነው የተቆጣጣሪነት ሚና አጋዥ ይሆናል ተብሎ ይታሰባል፡፡

የመጀመሪያው ዙር በቢሾፍቱ ከተማ አዱላላ ሆቴል፣ ሁለተኛው ዙር ደግሞ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ በቦንጋ ከተማ ከቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ከየካቲት 17-19 ቀን 2014 ዓ ም መከናወኑ የሚታወስ ሲሆን፤ይህ ሶስተኛ ዙር ምክክር መድረክ ደግሞ ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በባህርዳር ከተማ አቫንቴ (ብሉ ናይል) ሆቴል የሚደረግ ምክክር በግዥ ላይ የሚደረግ ሌብነትን የማክሰም ዘመቻ አካል ነዉ። የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን በሶስተኛ ዙር የምክክር መድረክ እየተሳተፉ ያሉ የዩኒቨርሲቲ ተሳታፊዎች የግዥ ስርዓት ላይ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ገልፀው ከጊዜ ጊዜ እያከናወኗቸው የሚገኙትን የግዥ ስርዓቶች በእውቀት ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ከማስቻል ባለፈ የግዥ ስርዓታቸውን ተቆራርጠው መምራት መጀመራቸውን ተሳታፊዎች ገልፀዋል፡፡

ባለስልጣኑ ተቋማትን ቀይ፣ ቢጫ፣ አረንጓዴ በማለት የሚፈርጅበትን ግልፅ መስፈርት በማስቀመጥ መገምገም የሚኖርበት ሲሆን ከዚህ በፊት በተቋሙ የወጡ አዋጆች፣ ሰርኩላሮችና መመሪያዎች ተሻሽለው ቢቀርቡ የግዥ ስርዓቱን ውጤታማና ቀልጣፋ ያደርገዋል ብለዋል፡፡  የገበያ ዋጋ መዋዠቅና አቅርቦትን ከገበያ ማጣት ለዩኒቨርስቲዎች ተግዳሮት መሆኑን ተሳታፊዎች ገልፀዋል፡፡ ለምክክር መድረኩ ውጤታማነት የዩኒቨርስቲዎች የግዥና ፋይናንስ እንዲሁም ኦዲት ዳይሬክትሮች መሳተፍ ይገባቸዋል ብለዋል፡፡  በተጨማሪም ኦዲተር ጀኔራል፣ የመንግስት ግዥ አገልግሎትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በምክክር መድረኩ መሳተፍ እንዳለባቸው ጨምረው ገልፀዋል፡፡ በሶስተኛ ዙር የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በግዥ አፈጻጸምና ንብርት አስተዳደር ዙሪያ በሚስተዋሉ ተግዳሮቶችና በወቅታዊ የገበያ ሁኔታ ዙሪያ ለከፍተኛ የትምህርት ተቋማት አመራሮች በተዘጋጀው የምክክር መድረክ ላይ በተጋባዥ እንግዶች ማላትም ማቴዎስ ኢንሰርሙ(ዶ/ር) የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አስተዳደርና ልማት ፕሬዝዳንት ግዥ ለአካባቢና ለዘላቂ ልማት፣በተመስገን ወንድሙ(ዶ/ር) ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በከፍተኛ ትምህርት የግንባታ ግዥና ውል አስተዳደር የሚስተዋሉ ችግሮች በሚል ርዕስ ጥናቶች እንዲሁም የዘመናዊ የንብረት አስተዳደርና ነዳጅ አጠቃቀም በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ በማቅረብ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

More Articles...