የመንግስት ግዥና ንብረት አስተዳደር ኤጀንሲ ከመንግስት ግዥና ንብረት ማሰወገድ አገልግሎት ጋር በመተባበር ከፌዴራል መንግስት ባለበጀት መ/ቤቶች፣ከአቅራቢ ደርጅቶች እና ከባለድርሻ አካላት ጋር የካቲት 20 ቀን 2009 ዓ.ም. በመንግስት ግዥና ንብረት ማስወገድ አገልግሎት የስብሰባ አዳራሽ የምክክር መድረክ አካሄደ፡፡
አቶ ይገዙ ዳባ የመንግስት ግዥና ንብረት ማስወገድ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በመክፈቻው ሥነ ሥርዓት ላይ እንደተናገሩት ለመንግስት ግዥና ንብረት ማስወገድ አገልግሎት ከተሰጠው ተልዕኮ ውስጥ የመንግስት መ/ቤቶች የሚጠቀሙባቸውን ተመሳሳይ ዕቃዎችና አገልግሎቶች እንዲሁም አገራዊ ስትራቴጂካዊ ጠቃሜታ ያላቸውን ዕቃዎችና አገልግሎቶች ከከፍተኛ ግዥ ኢኮኖሚያዊ ጠቃሜታ በሚያስገኝ መልኩ ግዥ መፈጸምና ውሳኔ የተሰጠባቸውን የመንግስት መ/ቤቶች ንብረቶችን በተቀላጠፈ አኳኋን በተመጣጣኝ ዋጋ በሽያጭ መፈፀም እንደሆነ አብራርተዋል፡፡
በመቀጠልም ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ይገዙ ዳባ አገልግሎቱ ግዥን ከመፈጸም ጎን ለጎን የመንግስት መ/ቤቶች ውሳኔ ሰጥተው እንዲወገዱ ለአገልግሎቱ የሚላኩት የተለያዩ ንብረቶችን በማስወገድ ረገድም የተለያዩ ንብረቶችን ሽያጭ በመፈፀም ከ470 ሚሊየን ብር በላይ ለመንግስት ግምጃ ቤት ፈሰስ ማድረጉንና በዚህ ግማሽ ዓመትም የተለያዩ ተሽከርካሪዎችን፣ልዩ ልዩ ጎማዎችን፣ዕቃዎችንና ቁርጥራጭ ብረታ ብረቶችን በማስወገድ በድምሩ ከ70 ሚሊየን ብር በላይ ለመንግስት ገቢ የተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አቶ ጆንሴ ገደፋ የመንግስት ግዥና ንብረት አስተዳደር ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር የውይይቱ ዓላማ የመንግስት ግዥና ንብረት አስተዳደር ኤጀንሲ ከመንግስት ግዥና ንብረት ማስወገድ አገልግሎት ጋር በጋራ በመሆን የዉይይት መድረኩ የተዘጋጀ መሆኑን፣በአሁኑ ጊዜ ትልቁ ችግር በመንግስት ግዥና ንብረት አከባቢ የሚስተዋለዉን የግንዛቤ ክፍተት ዙሪያ መንግስት ትኩረት የሰጠው ጉዳይ መሆኑን፣በአብዛኛው የሚታየው የአፈጻጸም ችግር ለመቅረፍ ኤጀንሲዉ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን፣ባለበጀት መስሪያ ቤቶች አመታዊ የግዥ ዕቅድ ስለማቅረብ፣ ለመንግስት ግዥና ንብረት አሰተዳደር ኤጀንሲ ስለተሰጠው ኃላፊነት፣የተጠያቂነት ሥርዓት ስለመዘርጋት የሚሉትን እና ሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ በዝርዝር ዉይይት አድርገዋል፡፡
በቀረበዉ የውይይት ሰነድ ዙሪያ በ2009 የመጀመሪያዉ ግማሽ በጀት ዓመት የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት፣ ያጋጠሙ ችግሮችና በቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ ላይ በዝርዝር ገለጻ ተደርገዋል፡፡
ለአንድ ቀን በቆየው የምክክር መድረክ የሁለቱም መ/ቤቶች ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው የፌዴራል መንግስት አካላት ተሳታፊ ሆነዋል፡፡
ከመ.ግ.ን.አ.ኤ. የሕዝብ ግንኙነትና ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት