የገንዘብ ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት ሩብ አመት አፈጻጸምን ገመገሙ።
(ጥቅምት 04/2018 ዓ.ም)፣ የገንዘብ ሚኒስቴርና በገንዘብ ሚኒስቴር ስር የሚገኙ ተጠሪ ተቋማት የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ አመት አፈጻጸምን በጋራ ገምግመዋል።
በግምገማው ወቅት የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ አመት አፈጻጸም በዋና ዳይሬክተሯ ክብርት ወ/ሮ መሰረት መስቀሌ የቀረበ ሲሆን በሩብ ዓመቱ መመሪያዎች፣ የስልጠና ሞጁሎች እና መሰል የአሰራር ስርዓቶች የተዘረጉበትና ወደ ትግበራ የተገባበት መሆኑን አመላክተዋል።
ክብርት ወ/ሮ መሰረት በገለጻቸው ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የአሰራር ስርዓቱን ሙሉ ለሙሉ ዲጂታላይዝ ለማድረግ ከፍተኛ ስራ የሰራ መሆኑን ጠቅሰው በዚህም የመንግስት ኤሌክትሮኒክ ግዥ (e-GP) በሁሉም የፌዴራል ባለበጀት መስሪያ ቤቶች ተግባራዊ መደረጉን፣ ዲጂታል ትምህርት (E- learning) መዘጋጀቱን፣ የኤሌክትሮኒክ ትምህርቱ አዳዲስ መመሪያዎችን እንዲያካትት መደረጉን፣ ዲጂታል የደብዳቤ መጻጻፊያ ተገባራዊ መደርጉን፣ ዲጂታል የአስተያየት መስጫ እና የቅሬታ መቀበያ ስርዓቶች ተግባራዊ መደረጋቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል።
ክብርት ወ/ሮ መሰረት አክለውም የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ (e-GP) ሥርዓት ትግበራን ወደ ክልሎች ለማውረድ ከፍተኛ ሥራ እየተሰራ እንደሚገኝና በዚህ ሩብ ዓመት ለድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር፣ ለሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ ለደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት፣ ለማዕከላዊ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት እንዲሁም ለሌሎች ክልሎች አስፈላጊውን ስልጠና እየተሰጠ እንደሚገኝ እና የመሰረተ ልማት ተግባራት እየተከናወነ እንደሚገኝ አብራርተዋል።
በተጨማሪም የመንግስት ኤሌክትሮኒክ ግዥን (e-GP) ከሌሎች ሲሲተሞች ጋር የማስተሳሰር ስራ መሰራቱንና የመንግስት ኤሌክትሮኒክ ግዥን (e-GP) ስርዓት በኢንሳ የደህንነት ኦዲት እንደተደረገለት በማብራሪያቸው የተካተተ ሲሆን የተጠናከረ ኦዲትና ክትትል ስርዓት መዘርጋቱንም በገለጻቸው አንስተዋል።

























